ረቡዕ 29 ሜይ 2013

መኢአድና ሰማያዊ ፓርቲ መንግስትን ለመክሰስ መረጃ እያሰባሰቡ ነው

እዚህ ፍትህ ካጣን ወደ ዓለምአቀፉ ፍ/ቤት እንሄዳለን 20ሺ ሰው ሲፈናቀል አላውቅም ማለት ተቀባይነት የለውም በቅርቡ የመላ ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ) እና ሠማያዊ ፓርቲ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በአማራ ተወላጆች ላይ የደረሠውን መፈናቀል አስመልክቶ ድርጊቱን በፈፀሙት የመንግስት ባለስልጣናት እና ተቋማት ላይ ክስ ለመመስረት መዘጋጀታቸውን ገልፀዋል፡፡ በዋናነት የክሡ መነሻ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ የደረሠው መፈናቀል ይሁን እንጂ ከአመት በፊት በደቡብ ክልል ጉራፈርዳ ወረዳ የደረሠው መፈናቀልና ያስከተለው ጉዳትም በክሡ እንደሚካተት ፓርቲዎቹ ተናግረዋል፡፡
ማስረጃዎችን አሠባስቦ በማቀናጀት ሃገር ውስጥ ለሚገኙ ፍርድ ቤቶች ክስ በመመስረት በኩል ደግሞ የቀድሞው የቅንጅት አመራር አባልና በአሁን ሠአት ከማንኛውም የፖለቲካ ድርጅት አባልነት ተገልለው በአለማቀፍ የህግ ባለሙያነት በመስራት ላይ የሚገኙት ዶ/ር ያዕቆብ ኃይለማርያም እንደሚሳተፉ ታውቋል፡፡ በክሱ አቀራረብና ባህሪ እንዲሁም ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማርያምን በቢሮአቸው አነጋግሯቸዋል፡፡ የክሡ ሂደት ምን ላይ ደረሠ? በሠማያዊ ፓርቲና በመኢአድ አነሣሽነት ነው ክሡ ሊመሠረት የታሠበው፡፡ ነገር ግን እስካሁን ክሡ አልተጀመረም፡፡ ማስረጃ ሠብስበን ከተጐዱት ሠዎች የውክልና ስልጣን ወስደን ወደ ስራው እንገባለን፡፡
አሁን ግን ገና ነው፤ የውክልና ስልጣኑም አልተዘጋጀም፡፡ በአካባቢው ያሉ ሠዎችን ማግኘት ያስፈልጋል፡፡ ስራው አሁን በውል ተጀመረ ማለት ባይቻልም በቅርቡ ሠዎች ወደዚያው ሄደው የተጐዱና የተፈናቀሉ ሠዎችን በመጠየቅና የደረሠባቸውን ጉዳት በማየት መረጃ እያሠባሠቡ ነው፡፡ ክሡን የምንመሠርተው ከዚያ በኋላ ይሆናል ማለት ነው፡፡ መጀመሪያ እንደሚታወቀው መረጃውን ማሠባሠብ ያስፈልጋል፡፡ በግልፅ ህግ መጣሡን በደንብ ማረጋገጥ ያስፈልጋል፡፡ እነዚህ ከተሟሉ በኋላ በቀጥታ ወደ ክሡ እንሄዳለን፡፡ መጀመሪያ የሠዎቹን ውክልና ሣታገኙ እንዴት ለመክሠስ እየተዘጋጃችሁ መሆኑን ገለፃችሁ?
መጀመሪያ ውክልናውን ማግኘታችሁን ማረጋገጥ አልነበረባችሁም? እንግዲህ ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት ይዘን የምንቀርበው በሁለት አይነት ነው፡፡ የወንጀልም የፍትሃ ብሄር ጉዳይም አለው፡፡ የወንጀል ጉዳይን በተመለከተ ማንኛውም ሠው እንደተጐጂው ሆኖ ለፍትህ አካል አቤት ብሎ፣ ፖሊሶች ጉዳዩን ከመረመሩና ማስረጃውን ካጠናቀሩ በኋላ ወደ አቃቤ ህግ ይመሩታል፡፡ አቃቤ ህግ ክስ ይመሠርታል ወይንም በቂ ማስረጃ የለኝም፤ ክስ አልመሠርትም ብሎ ሊተወው ይችላል፡፡ በቂ ማስረጃ ካለ ደግሞ ክስ መስርቶ ፍርድ ቤት ይቀርባል፡፡ በሁለተኛ ደረጃ በቀጥታ እኛ የምንሣተፍበት ደግሞ አለ። እነዚህ ሠዎች ከቤታቸው ተፈናቅለዋል፤ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፣ የንብረት መውደም ደርሶባቸዋል፣ ጤናቸው ታውኳል፣ ብዙ አይነት ጉዳት ነው የገጠማቸው፡፡ ያ ሁሉ በገንዘብ ተሠልቶ የሚገባቸውን ካሣ፣ ተጠያቂ የመንግስት አካላት እንዲከፍሉ ነው የሚደረገው፡፡ መኢአድና ሠማያዊ ፓርቲ ከተጐጂዎች መካከል በርካቶቹን ጠይቀው ፈቃደኝነታቸውን አረጋግጠዋል፡፡ የውክልና ስልጣን ከዚያ በኋላ ይመጣል ማለት ነው፡፡
ክሱ በዚህ አገር ያልተለመደ ዓይነት ይሆናል ብለው ነበር፡፡ ሊያብራሩት ይችላሉ? ብዙ ሠው የያዘ ቡድን አንድ አይነት ጉዳት ከደረሠበት አንዱ ብቻ ከሶ ፍርድ ካገኘ ሌሎቹም ክስ ሣይመሠርቱ ከውጤቱ ተጠቃሚ ሊሆኑ ይችላሉ። ይሄ በፈረንጆች “ክላስ አክሽን ሱት” ይባላል። ለምሣሌ የተፈናቀለው የአማራው ህብረተሠብ ተመሣሣይ በደል ነው የደረሠጁ እና ከእነሡ ውስጥ አንድ ሠው ብቻ ከሶ ፍርድ ካገኘ (ከረታ) ሌሎቹ የተጐዱ ሠዎች ክስ ሣይመሠርቱ፣ ለፍርድ ቤቱ ተመሣሣይ በደል እንደደረሠባቸው በማመልከት ብቻ ከፍርዱ እኩል ተጠቃሚ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ እንግዲህ ይህ በሃገራችን ብዙም አልተለመደም ግን እኛ ይህ አካሄድ በሃገራችን ይሠራል የሚለውን ልንፈትሸው ነው፡፡ ጉዳዩን በምሣሌ ማየት ይቻላል። አንድ መለያ ያለው የጥርስ ሣሙና ከገበያ ገዝተህ ሣሙናው የተመረዘ ቢሆንና ብዙ ሠዎች ተጠቅመውት ከተጐዱና አንድ ሠው ብቻ ክስ አቅርቦ ከኩባንያው ካሣ ካገኘ፣ ያንን የጥርስ ሣሙና ተጠቅመው ተጐጂ የሆኑ ሠዎች ከዚያ ፍርድ ውጤት ተጠቃሚ ይሆናሉ፡፡
እኛም በዚህ መልኩ ነው ክሣችንን የምንመሠርተው፡፡ በእያንዳንዱ ተጐጂ ስም ክስ የማቅረብ ሃሣቡ የለንም፡፡ ውክልናውን ከአንድ ሠው ብቻ ብታገኙም መክሠስ ትችላላችሁ ማለት ነው? አዎ በሚገባ ይቻላል፡፡ ውክልና የሠጠን ሠው ከፍርድ ሂደቱ በሚያገኘው ውጤት ተመሣሣይ ጉዳት ያጋጠማቸው ሁሉ ተጠቃሚ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ በዚህ መሠረት የአንድ ሠውም ውክልና የመንግስትን ተጠያቂ አካላት ለመክሠስ ያስችለናል፡፡ በአገራችን ይህን ለማድረግ የሚያስችል የህግ ማዕቀፍ አለ?
በህገ መንግሥቱም አለ፣ በወንጀለኛ መቅጫውም በፍትሃ ብሄር ህጉም አለ፡፡ ለምሣሌ በህገ መንግስቱ ላይ “ክላስ አክሽን ሡት” የሚባለውን በተመለከተ የተጠቀሠ አለ፡፡ በህገ መንግስቱ አንቀፅ 37 ላይ “ማንኛውም ቡድን ወይም ተመሣሣይ ጥቅም ያላቸውን ሠዎች የሚወክል ግለሠብ ወይም የቡድን አባል የመጠየቅና የማግኘት መብት አለው” ይላል፡፡ እንግዲህ ማንኛውም ግለሠብ፣ ተመሣሣይ ጥቅም ያላቸው የቡድን አባላትን ወክሎ የመጠየቅና የማግኘት መብት አለው፡፡ እንግዲህ ያ የሚወክለው ግለሠብ ጠበቃ ሊሆን ይችላል፡፡
የቡድኑ አባል ደግሞ ከተበዳዮች አንዱ ሊሆን ይችላል፡፡ በተለያዩ ምክንያቶች ከተጐጂዎች ውክልና የሚሠጣችሁ ሠው ብታጡስ…ምን ታደርጋላችሁ? የተሠሩ ወንጀሎችን ከአንዳንድ ሠዎች ጠይቀን፣ ያንን ሪፖርት ለፖሊስ እናቀርባለን። ፖሊሶች ለአቃቤ ህግ ያቀርባሉ፡፡ አቃቤ ህግ መረጃና ማስረጃዎችን መዝኖ ክስ ይመሠርታል፡፡ በፍትሃብሄር ካሣ ለማግኘት ግን እነሡ የውክልና ስልጣን ካልሠጡን አይሆንም፡፡ የወንጀሉ ክስ ግን እነሡ ውክልናውን ቢሠጡም ባይሠጡም ይቻላል፡፡ እኛ ሣንሆን በወንጀሉ አቃቤ ህግ ነው የሚከሠው፡፡ እኛ ግን እስካሁን የተረዳነው፣ ሠዎች የዚህ የፍትሃብሄር ክስን በተመለከተ በመኢአድና በሠማያዊ ፓርቲ አማካኝነት ክሡን ለማቅረብ ፍላጐት እንዳላቸው ነው፡፡ ዋነኛ ማስረጃችሁ ሊሆን የሚችለው ምንድን ነው? ዋነኛ ማስረጃ የሚሆኑት ተጐጂዎቹ ራሣቸው ናቸው፡፡ ለምስክርነት ይቀርባሉ፡፡ የመንግስት ባለስልጣናትም ለምስክርነት ይቀርባሉ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሣለኝ ይሄ ነገር ከባድ ወንጀል እንደሆነና መፈፀም እንደሌለበት፤ በአጥፊዎች ላይም መንግስት እርምጃ እንደሚወስድ አረጋግጠዋል፡፡ እሣቸውም በአካልም ሆነ ንግግራቸው በቪዲዮ ማስረጃነት ያለ ጥርጥር ይቀርባሉ፡፡ እርግጥ ማስረጃ በተለይ በተጐጂዎች ሲቀርብ የፍርሃቱ ነገር ሊኖር ይችላል፡፡ የክልሎቹ ባለስልጣናትም ሆኑ የፌደራሎቹ ሊያስፈራሯቸው ይችላሉ፡፡ ጥቃት የደረሠበት ሠው ደግሞ ይፈራል። አሁንም ጥቃት ውስጥ ያሉ ሠዎች ናቸውና ሊፈሩ ይችላሉ፡፡ ግን መኢአድና ሠማያዊ ፓርቲ እንዳረጋገጡልን በዚህ ጉዳይ ላይ ለመግፋት የሚፈልጉ ሠዎች አሉ፡፡ አንዱ የክሱ ጭብጥ “ዘር ማጥፋት” የሚል መሆኑን በሠጣችሁት መግለጫ ላይ ጠቅሳችኋል። ዘር ማጥፋት ሲባል ምንድን ነው? ዘር ማጥፋት በሚለው ክስ ለማቅረብ የሚያስችላችሁ የህግ ማዕቀፍ ይኖራል? ሁለት አይነት ወንጀሎች ናቸው፡፡ የዘር ማጥፋት የሚለው አንዱን ብሄረሠብ ወይም ዘር በከፊልም ሆነ ሙሉ ለሙሉ ለማጥፋት በማቀድ፣ በማሠብ ጥቃት መፈፀም ማለት ነው፡፡ ያን ጥቃት መፈፀም እንግዲህ ዘር ማጥፋት ሊሆን ይችላል። ዘር ማጥፋት (ዲፖርቴሽን) ሊሆን ይችላል፣ ማፈናቀልም ሊሆን ይችላል፣ ልጆች እንዳይወልዱና የዘር መተካካቱ እንዳይቀጥል ማድረግም ሊሆን ይችላል፡፡
ይሄ እንግዲህ በሠው ዘር ላይ የሚሠራ ወንጀል ነው – ጀኖሣይድ ወይም የዘር ማጥፋት ወንጀል ነው። አሁን እኛ እንደምንገምተው አማሮችን ከየክልሉ የማባረሩና የማፈናቀሉ ነገር ቆይቷል፡፡ ከበደኖ ጀምሮ አርባጉጉ፣ ጉራፈርዳ አሁን ደግሞ ቤንሻንጉል… ሌሎችም አሉ፡፡ ይሄ ቢደረግም የአማራን ዘር በከፊልም ሆነ በሙሉ ለማጥፋት ታቅዶ የሚደረግ ነው ወይ ለሚለው ማስረጃ የለንም፡፡ እነዚህ ሠዎች ለመፈናቀላቸው ከቦታ ቦታ መነቀላቸው፣ ንብረታቸውን ማጣታቸው፣ በአካላቸው ላይ ጉዳት መድረሡን እናውቃለን፤ ማስረጃውም አለ። እንግዲህ የዘር ማጥፋት ሣይሆን የዘር ማጥፋት ወንጀል የምንለው ከነበሩበት አካባቢ በዘራቸው ምክንያት ከተፈናቀሉ ነው፡፡ አንድ ሠው በዘሩ፣ በሃይማኖቱ ወይም በሚናገረው ቋንቋ ምክንያት ጉዳት ከደረሠበት በሠው ዘር ላይ የሚሠራ ወንጀል ነው፡፡ አሁን ሠዎች በአማራነታቸው፣ በዘራቸው በተቀነባበረ መልክ ለብዙ ጊዜ የዘር ማጥፋት ወንጀል በዚህ መልኩ ተፈፅሞባቸዋል፡፡
በአካባቢው አንድ ዘር ብቻ እንዲኖር ካለ ፍላጎት፣ እነዚህ ዘሮች (አማሮች)ከሚኖሩበት ተፈናቅለዋል፡፡ እና ይሄ ዘር ማጥፋት ይባላል፡፡ ሁለተኛው የዘር ማጥፋት ወንጀል የሚጀምረው አንድ ሠው በሃይማኖቱ፣ በዘሩ ምክንያት በተቀነባበረ መልኩ በሠፊው ግድያ፣ መፈናቀል፣ የመሣሠሉ ነገሮች ከተፈፀሙበት ነው። ሁለቱም በጣም ከባድ ወንጀሎች ናቸው፡፡ በአለማቀፍ ህግ መሠረትም በተመሣሣይ የወንጀል ፈርጅ ነው የሚቀመጡት፡፡ ተመሣሣይ ቅጣት ያስከትላሉ፡፡ እኛ አሁን በኢትዮጵያ የተፈፀመው ወንጀል የዘር ማጥፋት ነው ብለን ደፍረን ባንወጣም፣ የዘር ማጥፋት ወንጀል ለመሆኑ ምንም ጥርጥር የለውም፡፡ በተለይ በአማራዎች ላይ ያነጣጠረ ነው፡፡ እኔ በአማርኛ ተናጋሪዎች ላይ የሚለውን አልቀበለውም፡፡ ምክንያቱም ሁላችንም አማርኛ ተናጋሪዎች ነን፡፡ በዚህ መሠረት አማራዎች ለረጅም ጊዜያት በተቀነባበረ መልኩ ከተቀመጡበት ሲፈናቀሉ ኖረዋል፡፡ ይህ ደግሞ በአለማቀፍ ህግም በሃገራችን የወንጀለኛ መቅጫ ህግም ወንጀል ነው፡፡
“በዘር ማጥፋት” ወንጀል መክሠስ የሚያስችላችሁ የህግ ማዕቀፎች አሉ? በደንብ አሉ፡፡
አሁን እኔ እንዳጋጣሚ የወንጀለኛ መቅጫ ህጉን አልያዝኩትም እንጂ ይሄን የሚቀጣ አንቀፅ አለ፡፡ እንደውም የደርግ ባለስልጣናት በዘር ማጥፋት ወንጀል ተከሠው ነበር፡፡ በእርግጥ ክሡ ትክክል ነበር ማለት አይቻልም፡፡ ምክንያቱም ወንጀሉ ያነጣጠረው የፖለቲካ ቡድንን መሠረት አድርጐ ነበር፡፡ የዘር ማጥፋት ወንጀል የምንለው በሃይማኖት፣ በቋንቋ እና በዘር ሲሆን ብቻ ነው፡፡ በፖለቲካ እምነት መሆን የለበትም፡፡ ከዚህ አንፃር በህጋችን የዘር ማጥፋት ምንድን ነው የሚለው በግልፅ ተቀምጧል፡፡ የዘር ማጥፋት ወንጀል ማለት በሠው ዘር ላይ የሚፈፀም ወንጀል ወይም ማፈናቀል መሆኑ በህጋችን በግልፅ ተቀምጧል፡፡ የደርግ ባለስልጣናትም የተከሠሡት አንደኛ በዘር ማጥፋት፣ ሁለተኛ ደግሞ በዘር ማጥራት፣ ሶስተኛ ደግሞ በተራ ግድያ ተጠያቂ ሆነው ነበር፡፡ ጉዳዩ ከመሬት እና ከይዞታ ጋር የተገናኘ እንጂ የዘር ጥላቻ አይደለም የሚሉ አካላት አሉ? የዘር ጥላቻ ሆነም አልሆነም ዋናው ነገር መፈናቀላቸው ነው፡፡
ከቤት ንብረታቸው ብዙ ጊዜ የኖሩበትን ቦታ በግድ ማስለቀቅ ጥላቻ ቢኖረውም ባይኖረውም ወንጀል መሆኑ አይቀርም። በህገ መንግስቱ አንቀፅ 32፣ የመዘዋወር መብትን በተመለከተ “ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በህጋዊ መንገድ በሃገሪቱ ውስጥ የሚገኝ የውጭ ዜጋ በመረጠው የሃገሪቱ አካባቢ የመዘዋወርና የመኖሪያ ቦታ የመመስረት እንዲሁም በፈለገው ጊዜ ከሃገር የመውጣት ነፃነት አለው” ይላል፡፡ ደግሞ ለኢትዮጵያውያን ብቻ አይደለም፤ ለውጭ ዜጐችም ህጋዊ በሆነ መንገድ ወደ ኢትዮጵያ ከገቡ በፈለጉበት መኖርና ወደፈለጉበት መንቀሣቀስ ይችላሉ፡፡ ለውጭ ሃገር ሠዎች እንኳ መብቱ ተሠጥቷል፡፡ ማንኛውም ዜጋ በየትኛውም የሃገሪቱ ክልል ላይ መኖርና ሠርቶ መለወጥ ይችላል ማለት ነው፡፡ እርግጥ አንዳንድ የተከለሉ አካባቢዎች አሉ፡- እንደጦር ሠፈር፣ ቤተመንግስት፣ የእንስሣት ፓርኮች የመሣሠሉት … እዚያ ልግባ ቢሉም ልኑር ማለት አይቻልም፡፡ በተረፈ ግን ዘሩም ሆነ ቋንቋው ምንም ቢሆን የፈለገበት ቦታ ሄዶ የመኖር መብት እንዳለው ህገ መንግስቱ በግልፅ ይደነግጋል፡፡
አንድ ጊዜ ከጉራፈርዳ ስለተፈናቀሉ ሠዎች ጉዳይ በፓርላማው ጥያቄ ቀርቦ ነበር፡፡ ጠ/ሚ መለስ በወቅቱ እነዚህ ሠዎች ደን ይመነጥሩ ነበር ብለው መልስ ሠጡ፡፡ የዚህ አንደምታው የተወሠደው እርምጃ ትክክል ነው የሚል ነው፡፡ እነዚህ ሠዎች ዛፍ ይቆርጡ እንደሆነ ህግ ካለ በህግ ይጠየቃሉ፤ ጫካ ይመነጥሩ እንደሆነም እንደዚያው፡፡ አሁን አቶ ኃይለ ማርያም የተለየ መልስ ሰጥተዋል፡፡ አቶ መለስ ፍፁም ህጋዊ አድርገው የቆጠሩትን አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ህገወጥ መሆኑንና መደረግ እንደሌለበት፤ መንግስትም እርምጃ እንደሚወስድ ገልፀዋል፡፡ ከአካባቢው አማራዎች ብቻ ሣይሆኑ ኦሮሞዎችም የመፈናቀል እጣ ገጥሟቸዋል ተብሏል።
ይሄንንስ እንዴት ነው የሚያዩት? በእርግጥ ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ብለውታል፡፡ ነገር ግን በአማራዎች ላይ እየደረሰ ያለው መጠነ ሰፊ ነው፡፡ የቆየም ነው፡፡ በግብታዊነት ሰዎችን ማፈናቀል በፕላን የተሠራ የቆየ ድርጊት ነው። ሊፈፀም የማይገባው ወንጀል ነው የተፈፀመው፡፡ አሁን ክስ እንመሠርትባቸዋለን ከምትሏቸው ሃላፊዎች መካከል በህዝብ ተመርጠው የምክር ቤት አባላት የሆኑ አሉ፡፡ የእነዚህን ሰዎች ያለመከሰስ መብት ከግምት አስገብታችኋል? እንግዲህ አንድ የህዝብ ተወካይ ሊከሰስ የሚችለው ፓርላማው የዛን ሰው ያለመከሰስ መብት ሲሰርዝ ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ምናልባት እንደዚህ አይነት ያለመከሰስ መብት እንዳላቸውና እንደሌላቸው ማጣራት ይኖርብናል፡፡
ካላቸው ፓርላማ ወይም ምክር ቤት በዚህ በዚህ ወንጀል ምክንያት ያለመከሰስ መብታቸውን መሰረዝ አለበት ብለን ማመልከት አለብን፡፡ ያኔ ምክር ቤቱ ፍቃድ ከሰጠና ከሠረዘ ይከሰሳሉ ማለት ነው፡፡ በእርግጥ ይህ ሂደት ካልታለፈ መክሰስ አይቻልም። የትኛውም ፓርላማ እንዲህ አይነት ከባድና ግልጽ ወንጀል በሚፈፀምበት ጊዜ ያንን ያለመከሰስ መብትን ያሠርዛል፡፡ እኛም የትኛው ነው ያለመከሰስ መብት ያለው የሚለውን ካጣራን በኋላ፣ አስቀድመን ለምክር ቤቶቹ አመልክተን መብቱ እንዲሠረዝ እንጠይቃለን፡፡ ክሳችሁ የሚያካትተው በየትኛው ጊዜ እና በየትኛው የሃገሪቱ ክልል የተፈፀሙትን ወንጀሎች ነው? አሁን ለጊዜው ቤንሻንጉል እና ጉራፈርዳ የተከሰተውን ነው ያሰብነው፡፡ ሌላው በቀጠሩን ፓርቲዎች የሚወሰን ነው፡፡ በእርግጥ ድርጊቱ በብዙ ቦታዎች የተፈፀመ ነው፡፡ ግን ክስ የሚመሠረተው አንድም እንዲህ አይነት ድርጊት ለወደፊቱ እንዳይደገም ማስተማሪያ እንዲሆን ነው፡፡
ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እንዲቆም ለማድረግ ነው፡፡ ክስ ብዙ ጊዜ የሚመሠረተው ከክሱ ውጤት ሌላው እንዲማርና ተበዳዩ እንዲካስ ነው፡፡ ክሱ በአገር ውስጥ ፍ/ቤቶች ተቀባይነት ካጣ ወደ አለማቀፍ ፍ/ቤት እንሄዳለን ብላችኋል፡፡ ኢትዮጵያ የአለማቀፍ ፍርድ ቤት አባል ሳትሆን ክስ መመስረት ይቻላል? የክሱ አንዱና ዋናው አላማ ይህ ድርጊት ከእንግዲህ በማንም ኢትዮጵያዊ ላይ እንዳይፈፀም ነው፡፡ ሌላው ደግሞ ይሄ ክስ እዚህ ሊሳካልን ባይችል በአለማቀፍ ፍርድ ቤት ጉዳዩን የሚከታተሉ ኢትዮጵያውያን አሉ፡፡ ለነዚህ ኢትዮጵያውያን የዳበረ ማስረጃ ለመስጠት ነው፡፡ በአለማቀፍ ፍርድ ቤት ክስ ለመመስረት መጀመርያ የአገር ውስጡን ማጣራት አለብን፡፡ በአገር ውስጥ ፍትህ ከተነፈግን ወይንም የአገሩ መንግስት ሊሰማ ካልፈለገ ጉዳዩ ወደ አለማቀፍ ፍርድ ቤት ሊያመራ ይችላል፡፡ በፊት እንደተባለው ኢትዮጵያ የአለማቀፍ ፍርድ ቤት አባል አይደለችም፡፡ ለምን እንዳልሆነች እኔ በእውነት ሊገባኝ አይችልም፡፡ ምክንያቱም ከአፄ ኃይለስላሴ ጀምሮ በደርግም ዘመን ኢትዮጵያ አለማቀፍ ስምምነቶችን በመቀበል ንቁ ተሣትፎ ነበራት፡፡ የተባበሩት መንግስታትን ቻርተር ለመፈረም እኮ የመጀመሪያዎቹ ጥቁር ህዝቦች እኛ ነን፡፡
ኢህአዴግ ለምን ሊቀበለው እንዳልፈለገ አይገባኝም፡፡ ሆኖም ግን አገር ውስጥ ከባድ ወንጀል በሚፈፀምበት ጊዜ አባል አይደለችም፤ ስለዚህ አትከሰስም ተብሎ አይታለፍም፡፡ አባል ከሆነ በቀጥታ ፍርድ ቤቱ ጉዳዩ እንዲመረመር ያዛል፤ ተመርምሮ ክስ ይቀርብበታል። እንደ ኢትዮጵያ የፍርድ ቤቱ አባል ካልሆነ፣ ጉዳዩ ለተባበሩት መንግስታት የፀጥታ ምክር ቤት ቀርቦ፣ የፀጥታው ምክር ቤት ፍርድ ቤቱ ምርመራ እንዲያደርግና ክስ እንዲመሠርት ሊያደርግ ይችላል፡፡ አሁን ኢትዮጵያኖች የሚንቀሳቀሱበት መንገድ የተባበሩት መንግስታት የፀጥታው ምክር ቤት በጉዳዩ እጁን ያስገባና የአለማቀፍ ፍርድ ቤትን ምርመራ እንዲያደርግ ያዛል (ክስ እንዲመሠረት ሊያዘው አይችልም) ጉዳዩ ወደ ወንጀል ከመራ፣ ክሱ በተጐጂዎች ወይም ወኪሎች ሊቀርብ ይችላል፡፡ ኢትዮጵያ የአለማቀፍ ፍርድ ቤት አባል አለመሆኗ፣ ወንጀል ከተሰራ ከክስ ሊያስመልጣት አይችልም፡፡ እዚህ ፍትህ አለመኖሩ ከተረጋገጠ፣ በዚህ መልኩ ወደ አለማቀፉ ፍርድ ቤት እንሄዳለን፡፡
ክሱን የምትመሠርቱት ግለሰብ ባለስልጣናት ላይ ነው ወይስ ተቋማቱን ነው የምትከሱት?
ለምሣሌ ፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴርን እንደመስሪያ ቤት ነው ወይስ ሚኒስትሩን ነው? እኛ ተቋማቱን ነው የምንከሰው፡፡ እርግጥ ለተቋማቱ ተጠሪዎች አሉ፡፡ ተከሳሾች የሚሆኑት ደግሞ የክልል አስተዳዳሪዎች ብቻ አይደሉም። እንደውም ከፌደራል ጉዳይ መስሪያ ቤት ይጀምራል፡፡ እርግጥ አቶ ኃይለማርያም፤ ይሄ በኪራይ ሰብሳቢዎች፣ በሌቦች የተፈፀመ ነገር ነው፤ መንግስት አያውቀውም ብለው ነው መግለጫ የሰጡት፡፡ ይሄ ተአማኒነትና ተቀባይነት የሌለው ነገር ነው፡፡ ሃያ ሺህ ሰው ሲባረር አላውቅም ማለት የማንን ጐፈሬ ሲያበጥሩ ነበር ያስብላል፡፡ ፌደራል መንግስት ማወቅ ነበረበት፤ ባያውቅም የግዴታ ማወቅ ነበረበት። አላወቅሁም ካለም አለማወቅ ከተጠያቂነት ስለማያድን ማወቅ ይገባው ነበር፡፡ ባያውቅ እንኳ ማወቅ ስለሚገባው በህግ ይጠየቃል። በዚህ መሠረት ክሳችን ከፌደራል መንግስት ይጀምራል፡፡ ወደ ክልል አስተዳደሮች ይሄዳል። ከዚያም ወደ ወረዳ፣ ፌዴራል ፖሊስ እንዲሁም ከጉዳዩ ጋር ወደተነካኩት አካላት ይሄዳል፡፡
እንግዲህ ክሱ እንደገለጽኩት ገና አልተረቀቀም፤ በመነጋገርና መረጃ በማሰባሰብ ላይ ነው ያለነው፡፡ ሀገር ውስጥ ካሉት ፍርድ ቤቶች ምን ውጤት ትጠብቃላችሁ? የመጨረሻ ውጤቱስ ምን ይሆናል ብላችሁ ነው የምታስቡት? እኛ መቸም የምንጠብቀው ህጉ ይተገበራል ብለን ነው፡፡ የወንጀል ህጉም ሆነ ሌሎች ህጐች ይተገበራሉ ብለን ነው የምንጠብቀው፤ ግን የሚሆነው ሌላ ሊሆን ይችላል፡፡ ክሳችንን ውድቅ ሊያደርጉ ይችላሉ፡፡ ፍርድ ቤቱ ክሱን ተቀብሎ ካሣ የሚያስከፍል ወንጀል አላገኘንም ብሎ ክሱን ሊዘጋው ይችላል፡፡ ሆኖም ግን እኛ አስቀድሜ እንዳልኩት ይሄን ክስ ያነሳነው በአለማቀፍ ችሎት የቀረበ እንደሆነ፣ መጀመሪያ በሃገር ውስጥ ፍትህ ለማግኘት ተሞክሯል ወይ ተብሎ ስለሚጠየቅ ነው።
ፍትህ ለማግኘት ሞክሬ ፍትህ አላገኘሁም ወይም መንግስት ክሱን ለመቀበል ፈቃደኛ አልሆነም ካልክ፣ አለማቀፍ ፍርድ ቤት ጉዳዩን ሊቀበለው ይችላል፡፡ ለዚህ ድጋፍ እንዲሆን ነው ይህን ክስ የምንመሠርተው፡፡ በእውነት ፍትህ በሀገር ውስጥ አግኝተን ለእያንዳንዱ ካሣ ቢከፈል በጣም እገረማለሁ፤ እደነቃለሁ፡፡ ቢሆን ግን እሰየው ነው። ጉዳዩን እንዴት እንደሚያመልጡት አላውቅም፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ራሳቸው በደል ተፈጽሟል፣ ህግ ተጥሷል ካሉ እንዲሁ ዝም ብሎ ተነግሮ የሚታለፍ አይደለም፡፡ በደል ከተፈፀመ የግድ ለተበዳዩ የሚሆን ካሣ ይከተላል፡፡ ይሄ ሊሆን ግድ ነው፡፡ ይህ ባይሆን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ራሳቸው ተጠያቂ ይሆኑበታል፡፡ ወንጀል መሆኑን እያወቁ፣ በደል መፈፀሙን እያመኑ ዝም ብለው ካለፉት፣ ነገ በራሳቸው ቃል ተጠያቂ ይሆኑበታል፡፡

ሰኞ 6 ሜይ 2013

አሜሪካ የሽብር ህጉ አሰጋኝ አለች


አሜሪካ የሽብር ህጉ አሰጋኝ አለች
በሳምንቱ አጋማሽ በእነ አንዷለም አራጌና እስክንድር ነጋ ላይ የበታች ፍርድ ቤት የወሰነው ውሳኔ መጽናቱን ተከትሎ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ተቃውሞ አሰምቷል። ቪኦኤ ድምጻቸውን ያሰማቸው የሚኒስቴሩ ተጠባባቂ ቃል አቀባይ ፓትሪክ ቬንትል “ውሳኔው በጸረ ሽብር ህጉ ላይ ያለንን ስጋት ያጠናክረዋል” ሲሉ ተደምጠዋል።
“በጋዜጠኛ እስክንድር ነጋና በእነ እንዷለም አራጌ ላይ የተላለፈው ፍርድ በመጽናቱ አሜሪካ በጥልቅ ቅር ተሰኝታለች” ያሉት ቃል አቀባዩ ውሳኔው መንግስት የሚተቹትን ሁሉ ለፍርድ እንደሚያቀርብ አመላካች ነው ብለዋል።
ሰዎች በነጻነት የመናገርና የማሰብ መብት እንዳላቸው የጠቆሙት ቃል አቀባዩ ኢትዮጵያ በህገ መንግስቷ ያሰፈረችውን የሰብአዊ መብቶችንና የዲሞክራሲ መብቶችን ማክበር የወደፊቱ ግቧ እንደሆነ አመልክተው “ኢትዮጵያ እነዚህን መሰረታዊ መብቶቻቸውን ስለተጠቀሙ ያሰረቻቸውን በሙሉ እንድትፈታ ደጋግመን እንጠይቃለን” ብለዋል። አሜሪካ በሽብርና ከሽብር ጋር ተያያዥነት ባላቸው ጉዳዮች ኢህአዴግን በግንባር ቀደም የምታግዝና ዘመናዊ የመረጃ መሰብሰቢያ መሳሪያ የምታቀርብ አገር መሆኗ የሚታወቅ ነው።
የእስክንድር ነጋ ባለቤት ሰግታለች
ለፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ አቅርበው ከነበሩት መካከል አንዱ የሆነው እስክንድር ነጋን ወደ ዝዋይ ማረሚያቤት ወይም ከአዲስ አበባ ውጪ ወደ ሌላ ማረሚያ ቤት ለማዛወር መታሰቡን ባለቤቱ ሰርካለም ስጋቷን እንደገለጸች ሪፖርትር አስታውቋል። ጋዜጣው ዝርዝር ባያቀርብም እስክንድር ወደ ዝዋይ ከተዛወረ ባለቤቱና ልጁ እሱን ለመጠየቅ እንደሚቸገሩና ምን አልባትም ችግሩ አሳሳቢ ሊሆን እንደሚችል ይገመታል። እነ እስክንድር ነጋ ላይ የ18 ዓመት ፍርድ ያጸኑት ዳኛ ዳኜ መላኩ ናቸው።
ዳኜ መላኩ ውሳኔውን ካሳወቁ በኋላ ከፍተኛ የሃዘን ስሜት ችሎቱ ውስጥ ይታይ ነበር። ፍርደኞቹ ወደ እስር ቤት ሲመለሱ ድምጽ አውጥተው ስሜታቸውን የገለጹላቸው እንደነበሩ ሪፖርትር በደፈናው ግለጿል። እስክንድር እጁን ወደ ፈጣሪው በማንሳት “እውነት ተደብቃ አትኖርም” ሲል መናገሩን የተለያዩ ሚዲያዎች ዘግበዋል”፡፡
 የሽብር ህጉ የፕሬስ ነጻነትን አውድሟል ተባለ
ባለፈው አርብ በዓለም ተከብሮ የዋለውን የዓለም የፕሬስ ነጻነት ቀን አስመልክቶ መግለጫ ያወጣው ሂውማን ራይትስ ዎች “የኢትዮጵያ የሽብርተኞች ህግ የፕሬስ ነጻነትን አውድሟል” አለ። እስረኞች እንዲፈቱ ለማድረግ እንደሚሰራ አስታውቋል።
ከመግለጫው በተጨማሪ የድርጅቱ የናይሮቢ ጥናት አቅራቢ ላቲቪያ ቤደር የሽብር ህጉ በረቂቅ ደረጃም ሆነ ህግ ሆኖ በስራ ላይ ከዋለበት ጊዜ ጀምሮ የመናገር መብትን የሚነፍ መሳሪያ መሆኑን ተናግረዋል። ለቪኦኤ ቃላቸውን የሰጡት ላቲቪያ ድርጅታቸው የምዕራቡን ዓለም የኒዖ ሊብራል ሃሳብ አቀንቃኝ ስለሆነ ነው በተደጋጋሚ ኢህአዴግን የሚቃወመው በሚል ስለሚሰነዘረው ለተጠየቁት “ይህ በማንኛውም መልኩ ርዕዮተ አለማዊ ጉዳይ አይደለም፤ ጥሪያችን ስለ መሰረታዊው የሰብአዊ መብት መከበር ነው። ኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፍ ደረጃ የምናደርገው የመብት ጥሪ ነው። በኢትዮጵያ ይበልጥ የሚያሳስበን ጸረ ሽብር የተባለ ሀግ ጸድቆ ጋዜጠኞችን ለማፈን ጥቀቅም ላይ መዋሉ ነው” የሚል ምላሽ ሰጥተዋል።
የሂይውማን ራይትስ ዎች አጥኚ ላቲቪያ ቤደር ድርጊቱን ከመቃወም ባለፈ ጫና በመፍጠር የታሰሩት የፖለቲካ አስረኞችና ጋዜጠኞች እንዲፈቱ እንደሚሰሩ ተናግረዋል። ለቪኦኤ በሰጡት ቃል እንዳስታወቁት “አገራቱን በሚረዱ ወዳጅ አገሮችና ለነጻነት የሚቆረቆሩ ተጽዕኖ ፈጥረው እስረኞቹን እንዲያስፈቱ በየጊዜው እንወተውታለን” ብለዋል። በፕሬስ ነጻነት ቀን ይፋ እንደሆነው በኢትዮጵያ 11 ጋዜጠኞች በሽብር ህግ ተከሰዋል። ስድስቱ በሌሉበት ክስ የተመሰረተባቸው ሲሆን፣ አምስቱ ወህኒ ቤት የሚገኙት ናቸው። ከአምስቱ መካከል ሶስቱ ተፈርዶባቸዋል። ሁለቱ ዮሴፍ ጌታቸውና ሰለሞን ከበደ የፍርድ ሂደታቸውን እየጠበቁ ነው።
ኤርትራ ካሰረቻቸው ጋዜጠኞች መካከል የተገደሉ አሉ
የኤርትራው ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ካሰሯቸው ከ10 በላይ ጋዜጠኞች መካከል እስር ቤት በሚያሳዝን መልኩ የሞቱ እንዳሉ ታማኝ ምንጮች እንዳረጋገጡለት የሂውማን ራይትስ ዎች የአፍሪካ ምክትል ሃላፊ ተናግረዋል። ሃላፊው ለቪኦኤ የናይሮቢ ዘጋቢ እንደነገሩት ኤርትራ ውስጥ የታሰሩት ጋዜጠኞች ጉዳይ ከፍተኛ ስጋት ፈጥሯል።
እስረኞቹ ቤተሰቦቻቸውን አያገኙም፣ የት እንዳሉ በውል አይታወቅም፣ በዜግነት ስዊዲን የሆነው ዳዊት ይስሃቅን ጨምሮ ሁሉም እስረኞች በህይወት ስለመኖራቸው ቤተሰቦቻቸው ተስፋ በቆረጡበት ወቅት ሃላፊው ጉዳዩ ለአፍሪቃ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ስለቀረበ ይፈታሉ የሚል ተስፋ እንዳላቸው ተናግረዋል።
በተመሳሳይ ከታህሳስ 2006 ጀምሮ ኢትዮጵያ ያሰረቻቸውን ተስፋ ልደት ኪዳኔና፣ ተስፋ እግዚ የተባሉትን ሁለት የኤርትራ ተወላጆች ጉዳይም ሃላፊው አንስተዋል “ጋዜጠኞቹ በኮሚኒካዶ ታስረዋል” ያሉት ሃላፊው እስረኞቹ በጠበቃ መወከልና በቀይ መስቀል ሊጎበኙ እንደሚገባ አመልክተዋል። ጋዜጠኞቹ በቁጥጥር ስር የዋሉት የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ኤርትራ ዘልቆ ከገባ በኋላ ነበር። በወቅቱ ከፍተኛ መስዋዕትነት ከተከፈለና ጦርነቱ ከተጠናቀቀ በኋላ አቶ መለስ ጦሩ የያዘውን ቦታ ለቆ እንዲወጣ ማዘዛቸው አይዘነጋም።
በተዛማጅ ዜና በዓለም አቀፍ ደረጃ በ2012 ብቻ 121 ጋዜጠኞች መገደላቸውን በመግለጽ ለጋዜጠኞች ጥበቃ እንዲደረግ ዩኔስኮ ጥሪውን አቅረቧል። ዩኔስኮ ይህንን ጥሪ ያስተላለፈው የፕሬስ ነጻነት ቀንን አስመልክቶ ነው።
የአቶ አስግደ ገብረስላሴ ሁለተኛ ልጅ ታሰረ
የህወሀትን የበረሀ ትግል ታሪክ የሚዘክረውን ገሀዲ ቊጥር አንድ፣ ሁለት እና ሶስት የሚሉ መጽሀፎችን ከመጻፍ በተጨማሪ በትግራይ ውስጥ የሚፈጸሙ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶችን በማጋለጥ የሚታወቁት አቶ አስገደ ገብረስላሴ ሁለተኛ ልጅ ታስሯል።
የ28 አመቱ የማነ አስገደ ገብረስላሴ የሶፍት ዌር ኢንጂነረግ ምሩቅ ሲሆን፣ በውቅሮ በመምህርነት ሙያ ተቀጥሮ ነበር። አዲሱን ስራውን ሲጀምር አቶ አስገደ ልጅ መሆኑ በመታወቁ በቅጣት ወደ በረሀ ተመድቦ እንደነበር አባቱ አቶ አስገደ ገልጸዋል።
እናቱ ሻለቃ ግደይ ወ/ሚካኤል ልጃቸውን አያቱ ወደ ሚኖሩበት አዳህላይ ወደምትባል ቀበሌ ለህክምና መውሰዳቸውን ተከትሎ በቀበሌው የሚገኘው ትምህርት ቤት በመቃጠሉ የህወሀት ባለስልጣናት ህዝቡን ሰብስበው “ትምህርት ቤቱን ያቃጠለው አቶ አስገደ የሚባል የአረና ትግራይ ድርጅት አባል ልጅ ነው” በማለት ሊወነጅሉ ሲሞክሩ ህዝቡ “ሀሰት ነው ” በማለት በመቃወሙ ባለስልጣናቱ ሳይሳካላቸው እንደቀረ አቶ አስገደ ገልጸዋል። ስብሰባው ከተበተነና ህዝቡ ወደ ቤቱ ከገባ በኋላ ፖሊሶቹ ልጃቸውን አስረው መውሰዳቸውን ተናግረዋል።
ሌላው በእስር ላይ የሚገኘው የ26 አመቱ አክህፎም አስገደ 06 እየተባለ ከሚጠራው ድብቅ እስር ቤት ወጥቶ ወደ ሌላ እስር ቤት መዛወሩን አቶ አስገደ ገልጸው፣ አለም ባደረገው ጫና ትናንት ለመጀመሪያ ጊዜ ልጃቸውን በአይናቸው ለማየት እንደቻሉ እና ከወር በኋላም ፍርድ ቤት እንደሚቀርብ አክለዋል።
አቶ አስገደ በትግራይ ክልል ውስጥ በርካታ ቤርሙዳ እየተባለ የሚጠራ እስር ቤት መኖሩን አውስተዋል። “የእነሱ ልጆች በህዝብ አንጡራ ሀብት ይማራሉ፣ የኛ ልጆች ይህን የተበላሸ ኑሮ ችለው በኖሩ በእንዲህ አይነት እስር ቤት ማሰቃየት ከዚህ በላይ የሰብአዊ መብት ጥሰት የለም ብለዋል። (ዘገባው የኢሳት ነው)